Tsion Assefa3 reviews12 followersFollowFollowApril 8, 2022ዛሬ ላይ ቆመን ታሪክን የኋሊት ስንቃኝ በዛሬ ሚዛን ልንመዝነው ያሰኘናል። ለዚህም ነው ፖለቲካና ማህበራዊ ህይወት ከዘውግ ማንነት ጋር በጥብቅ በተሸመነባት ሃገር ላይ ቆመን ትናንታችንን ልንገመግም ስንነሳ ሌሎች መመዘኛዎችን በሙሉ ችላ በማለት ዘውግን እንደብቸኛ ገዢ factor ልንወስድ የምንነሳው። ነገር ግን የሰውን ልጅ ተፈጥሮ ስንመለከት ከብዙ የማንነት ክሮች የተሰራ፤ የብዙ ቡድኖችም አባል ነው። እንደአስፈላጊነቱም እነዚህን ክሮች እየመዘዘ፣ ገናና እና ንዑስ እያደረገ ህይወቱን ይመራል። በነዚህ የተለያዩ የማንነት ክሮቹ የተነሳም ከተለያየ ቡድን ከመጡ ሰዎች ጋር lived experience ይጋራል፣ ይነጋገራል፣ ይግባባል፣ ይተሳሰባል። በዚህም መንገድ ግለሰቦች ሃገር ያቆማሉ። ከዛም አለፍ ሲል ባህር የተሻገረ ትስስር መስርተው አለም አቀፋዊነትን ይሰብካሉ። ግን አንድን ማንነት ነጥለን ለፖለቲካ መሰረት ብሎም የግለሰቦች ብቸኛ መገለጫ እንዲሆን በህግም ጭምር ስንቃኘው ምን ይፈጠራል?? ግለሰቦች ሌሎች የማንነት ክሮቻቸውን ሁሉ እንደአስፈላጊነቱ ይበጥሳሉ። ከምክኒያታዊነት ተፋተው ጽንፍ የረገጡ አቋሞችን በመያዝ በገዛ የስሜት ህዋሳቶቻቸው ያወቋቸውን ሃቆች ሳይቀር በመካድ እውነታን እኛና እነሱ በሚል የተንሸዋረረ መነጽር ለማየት ይገደዳሉ።የመስከረም አበራ 'የዘውግ ፖለቲካ ስረ-መሰረቶች' የተሰኘ መጽሃፍ የዛሬዋ ኢትዮጵያ ላይ ቆሞ ምን፣ ለምን፣ እንዴት፣ ወዴት እያለ ቃላቶቻችንን፣ ትርክቶቻችንን፣ መፈክሮቻችንን፣ ርዕዮተ አለሞቻችንን...ያለተጠየቅ ሃቅ ናቸው ብለን የተቀበልናቸውን ሃሳቦች ከአለም ከታሪክ ማህደር ምሳሌ እያነሳ እና ከማህበራዊ ሳይንስ ንድፈ ሃሳቦች እያጣቀሰ ይሞግታል። ሃገሪቱ ለምትመራበትን የዘውግ ፖለቲካ መሰረት የሆኑትን የግዛት፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት እሳቤዎች እያነሳ በሃገሪቱ ከተፈጠሩ ታላላቅ ኢኮኖሚያዊ፣ ታሪካዊ እና ፖለቲካዊ ክስተቶች ጋር በማስተሳሰር የትርክት ማስተካከያዎችንም ያቀርባል።Scholarly literature በአማርኛ ቋንቋ ማዘጋጀት የትምህርት ስርዐቱን በእንግሊዝኛ ባደረገ ሃገር ውስጥ ትልቅ ራስምታት ሊያስከትል የሚችል መሆኑን እገምታለሁ። በመሆኑም የፀሃፊዋ ይህን ሃላፊነት ለመውሰድ መነሳት በሙያ/እውቀት ደረጃ እኩዮቿ ከመነበብ በዘለለ ህዝብ ጋር እንዲደርስ ካላት ፍላጎት እንደሆነ በማሰብ አድንቄ አልፌአለሁ።የመጀመሪያዎቹ 2/3 ምእራፎች የተወሰኑ የሃሳብ መደጋገሞች ቢኖሯቸውም ከዛ በሚመጡት ምዕራፎች ግን ከጽንሰ ሃሳቦች ተሻግሮ ወደ ታሪክና አሁናዊ እውነታ ስለሚሄድ ስነጽሁፋዊ ውበትንም እየተላበሰ ስለሚመጣ ለማንበብም እንዲሁ እየቀለለ ይሄዳል።ይህ መጽሃፍ እንድናስብ፣ እንድንጠይቅ፣ ታሪክን እንድንመረምር ምሳሌ ሆኖ የሚያሳይ እና የሚያደፋፍር በመሆኑ በክፍት አዕምሮ እየተደጋገመ ሊነበብ የሚገባ፤ at face value ከመውሰድ ባለፈም ሊመረመርና ተጠየቅ ውስጥ ሊገባ እንዲሁም የምሁራዊ ውይይቶችም ርዕስ ሊሆን የሚገባ ነው ብዬ አምናለሁ። በፖለቲካ አቋማቸው ከመስከረም በተቃራኒ የቆሙ ምሁራንም ሃሳቧን በሃሳብ፣ ማስረጃዎቿንም በማስረጃ እንዲሞግቷት እመኛለሁ።